Thursday, December 27, 2012

በሎሚ ዲሳ ወረዳ የፖሊስ አባላት ከህዝብ ጎን በመቆማቸው ስብሰባ እንዳይካፈሉ ታገዱ


በደቡብ ክልል በዳውሮ ዞን በገሳ ከተማ በተጠራው የመንግስት ሰራተኞች ስብሰባ ላይ የሎማ ዲሳ ህዝብን አዲስ የወረዳ ጥያቄን በመደገፍ ንግግር የዳረጉት የሀምሳ አለቃ ሽታየ ከታሰሩ በሁዋላ፣ ሌሎች የወረዳው ፖሊሶች ዛሬ በተጠራው ስብሰባ ላይ እንዳይካፈሉ ታግደዋል።
የዞኑ ባለስልጣናት ለዲሳ ህዝብ ወረዳ አያስፈልገውም በማለት መናገራቸውን ተከትሎ አምሳ አለቃው ” ወረዳ ለህዝብ ባያስፈልግ ኖሮ ያኔ ለሲዳማ 9 ለወላይታ 5 እና ለሌሎችም ሁሉ እንደየአቅማቸው ሲታደል ለምን ይቀር አላሉም? ወረዳ ለህዝብ አያስፈልግም የሚለውን እኛ መናገር አንችልም ህዝቡ ይገለናል፣ ከፈለጋችሁ ራሳችሁ ሂዱና አሳምኑ” በማለት መመለሳቸው መዘገቡ  ይታወቃል።
የዞኑ የገጠር ፖለቲካ አደረጃጀት ሀላፊ አቶ ተስፋየ መጊሶ ” ይህ የጥገኞች  አስተሳሰብ ነው” በማለት መመለሳቸውን ተከትሎ አምሳለቃው፣ ” እኔ ጥገኛ አይደለሁም የመናገር ነጻነት ያለ መስሎኝ ነው ስለዚህ ጥገኛ ስብሰባ ምን ያደርግለታል፡” በማለት አዳራሹን ለቀው ወጥተዋል። ሌሎች ተሰብሳቢዎችም እርሳቸውን ጥለው መውጣታቸው ይታወሳል።
በአምሳለቃው ንግግር ያልተደሰቱት ባለስልጣናቱ በዛሬው እለት የወረዳው የፖሊስ አባላት ወደ ስብሰባ እንዳይገቡ ተከልክለዋል።
በዛሬው አለት የተገኙት ተሰብሳቢዎች የሎማ ዲሳ ህዝብ የወረዳ ጥያቄ መፍትሄ ካላገኘ እንዳይስማሙበት በአንድ ድምጽ መግለጻቸው ታውቋል።
ጉዳዩን በማስመልከት ጥያቄ ያቀረብንላቸው በስዊድን አገር የሚኖሩት የአካባቢው ተወላጅ መምህር ፍስሃ ተስፋዬ መንግስት ህዝቡን እርስ በርስ ለማጋጨት እየሞከረ ነው በማለት ወቅሰዋል።

    No comments:

    Post a Comment