Friday, August 22, 2014

የግንቦት 7 ሕዝባዊ ስብሰባዎች በዓለም ሃያ ስድስት ታላላቅ ከተሞች

ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ በመላው ዓለም ላይ ከሚገኙ አባላት፣ ደጋፊዎቹና በአጠቃላይ ከኢትዮጵያውያን ጋር በወቅታዊ ሁኔታዎች ላይ ለመመካከር ዝግጅቱን አጠናቋል።

በዚህም መሠረት ከዚህ በታች በተዘረዘሩት 26 የዓለም ታላላቅ ከተሞች ሕዝባዊ ስብሰባዎችን ተጠርቷል።

በላስቤጋስ ዩ ኤስ አሜሪካ ረቡስ ኦገስት 27 ቀን
በሂውስተውን ዩ ኤስ አሜሪካ ቅዳሜ ኦገስት 30 ቀን
በአትላንታ ዩ ኤስ አሜሪካ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
በዋሺንግተን ዲሲ ዩ ኤስ አሜሪካ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
በቦስተን ዩ ኤስ አሜሪካ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
በሎስ አንጀለስ ዩ ኤስ አሜሪካ ቅዳሜ ሴፕተምበር 6 ቀን
በሳንቲያጎ ዩ ኤስ አሜሪካ እሁድ ሴፕተምበር 7 ቀን
በቶሮንቶ ካናዳ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
በካልጋሪ ካናዳ ሴፕቴምበር 1 ቀን
በደርባን ደቡብ አፍሪቃ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
በጆሃንስበርግ ደቡብ አፍሪቃ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
ቬሪኒንፍ ደቡብ አፍሪቃ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
ሩስተምበርግ ደቡብ አፍሪቃ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
ፍራክፈርት ጀርመን ቅዳሜ ኦገስት 30 ቀን
ሙኒክ ጀርመን እሁድ ኦገስት 31 ቀን
ሄልሲንኪ ፊንላንድ ቅዳሜ ኦገስት 30 ቀን
አምስተርዳም ኒዘርላንድስ ቅዳሜ ሴፕተምበር 13 ቀን
ኦስሎ ኖርዌይ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
ለንደን እንግሊዝ ቅዳሜ ሴፕተምበር 6 ቀን
ስቶክሆልም ስዊድን ቅዳሜ ሴፕተምበር 6 ቀን
ፐርዝ አውስትራሊያ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
ሜልቦርን አውስትራሊያ እሁድ ሴፕቴምበር 7 ቀን
ቴላቪቭ እስራኤል ሐሙስ ሴፕቴምበር 11 ቀን
ብራሰልስ ቤልጂየም እሁድ ሴፕቴምበር 14 ቀን
ኦክላን ኒዩ ዚላንድ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
ሲኡል ደቡብ ኮርያ እሁድ ኦገስት 31 ቀን
በእነዚህ ስብሰባዎች ሁሉ የንቅናቄዓችን ዋና ፀሐፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ ሥራዎች ይወሳሉ። ወያኔን ማስወገድ በሚቻልበት ስልቶች ላይ ውይይት ይደረጋል። እስከዛሬ ድረስ ንቅናቄዓችንን ለመቀላቀል የተቸገራችሁ ወገኖች ይህንን አጋጣሚ እንድትጠቀሙበት ጥሪ እናደርጋለን። በማናቸውም ምክንያት አባል ሳይሆን ደጋፊ መሆን ለምትፈልጉ ወገኖቻችንን የደጋፊዎች ምዝገባ ሥርዓት አዘጋጅተናል፤ እድሉን ተጠቀሙበት።

ኑ! ኢትዮጵያ አገራችንን፣ ኢትዮጵያዊ ወገናችንን እና ራሳችን ነፃ ለማውጣት እና በሀገራችን ፍትህ እንዲሰፍን ለማድረግ የሚደረገውን ትግል ይቀላቀሉ። ከዘወትር የህሊና ወቀሳ ይገላገሉ። ለዚህ ትግል ሁሉም የሚያበረክተው ነገር አለ። ስለሆነም በአቅራቢያዎ ወደሚደረገው የግንቦት 7 ስብሰባ ይምጡ፤ ጥያቄዎች ካልዎት ይጠይቁ።

አሁን ወሳኝ የትግል ምዕራፍ ላይ እንገኛለን። ትግላችን ሶስት የትግል ስልቶችን ያስተባበረ ነው – ሕዝባዊ ተቃውሞ፣ ሕዝባዊ እምቢተኝነት እና ሕዝባዊ አመጽ። ትግላችን በአገር ውስጥም ከአገር ውጭም ነው።

በውጭ አገራት የሚገኙ ኢትዮጵያዊያን ከድጋፍ ሰጪነት ወደ ተግባራዊ ተሳትፎ የተሸጋገሩበት ወቅት ነው። ይህ ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባዋል። የወያኔ ድርጅቶችና የወያኔ ሹማምንት በየትኛው አገር ተዝናንተው እንዲኖሩና እንዲነግዱ አንፈቅድላቸውም። በእነዚህ ስብሰባዎች ስለዚህ ጉዳይ ይመከራል።

ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች ለኢትዮጵያ ክብርና ነፃነት ሕይወታቸውን ለመሰዋት ተነስተዋል። በእነዚህ ስብሰባዎች የአርበኛ ወጣቶቻችንን ጥረት እንዘክራለን። ሺዎች እንዲቀላቀሏቸው ጥሪ እናደርጋለን። በሁሉም ስብሰባዎች በአገር ውስጥም በውጭ አገርም የሚገኝ ኢትዮጵያዊ ወጣት ትግሉን እንዲቀላቀል ጥሪ ይደረግለታል።

በሁሉም ስብሰባዎች ለኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት አባላት ጥሪ ይደረጋል። የሠራዊቱ መሪዎች የፋሽስት ወያኔ ባለሟሎች ቢሆኑም ሠራዊቱ ግን ከኢትዮጵያ አብራክ የወጣ ኢትዮጵያዊ ነው። ሠራዊቱ የወያኔ መጠቀሚያ ከመሆን የነፃነት ታጋዮችን እንዲቀላቀል፤ ያ ካልተቻለም ለወያኔ ሥልጣን እንዳይሞት፤ ወገኑን እንዳይገል ጥሪ ይደረግለታል።

መጥተው የእነዚህ ታሪካዊ ስብሰባዎች አካል ይሁኑ።

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

Tuesday, August 19, 2014

“አሸባሪነት” በወያኔ አገዛዝ ሥር ባለችው ኢትዮጵያ


በአገራችን፣ በወያኔ አገዛዝ መደበኛ ትርጉማቸውን ከሳቱ በርካታ ቃላት መካከል “የሽብር ድርጊት“ እና ”አሸባሪ“ የሚሉት ግንባር ቀደሞቹ ናቸው። ሰፊ ተቀባይነት ያለው የአሸባሪ ትርጉም “የሽብር ድርጊቶችን የሚፈጽም ሰው ወይም ድርጅት” ማለት ነው።
“የሽብር ድርጊቶች” የሚባሉት ደግሞ የተለመዱ ጥቃቶችን ሳይሆን የሀይማኖት፣ የፓለቲካ ወይም የርዕዮተዓለም ግብ ለማሳካት ሲባል በሰዎች ላይ ፍርሀትን ለማንገስ፤ በሰላማዊ ዜጎች ላይ የሚደርሱ አስከፊ ጥቃቶችን ነው። የሽብር ድርጊቶችን ሰላማዊውን ሕዝብ ጭዳ የሚያደርጉ በመሆኑ በጥብቅ ሊወገዙ ይገባል። ዓላማን በሽብር ድርጊቶች ማስፈፀም ተቀባይነት የሌለው ተግባር ነው።
በወያኔ መዝገበ ቃላት ግን “ሽብርተኛ” እና “የሽብር ድርጊቶች” በዘፈቀደ የሚነገሩ ተራ ቃላት ሆነዋል። ስለአገራቸው እና ስለትውልድ የሚጨነቁ፤ ሀሳባቸው በነፃነት የሚያራምዱ፤ የወያኔን ፕሮፖጋንዳ እንደ በቀቀን የማይደግሙ ዜጎች “አሸባሪዎች” እየተባሉ ወደ እስር ቤቶች እየተወረወሩ ነው። ጋዜጠኞች፣ ጦማርተኞች፣ ፍጹም ሰላምተኛ አማኞች እና ሰላማዊ ፓለቲከኞች በሽብርተኞች ዝርዝር ውስጥ ቀዳሚውን ሥፍራ የያዙ ናቸው።
በአንፃሩ ደግሞ እውነተኛው አሸባሪ ህወሓት፣ የመንግሥትን ሥልጣን ይዞ መላውን የኢትዮጵያ ሕዝብ ማሸበሩን በስፋት ተያይዞታል። ህወሓት ዘረኛ ርዕዮተ ዓለሙን ለማስፈፀም ሲል ባለፉት ሠላሳ አምስት ዓመታት ውስጥ የፈፀማቸው የሽብር ድርጊቶች ተዘርዝረው አያልቁም። የህወሓት የሽብር ድርጊቶች ዓላማ የኢትዮጵያን ሕዝብ በፍርሀት አደንዝዞ መግዛት ነው። ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ “አሸባሪ” የሚለውን ቃል ራሱ በማሸበሪያ መሣሪያነት እያዋለው ነው። ይህ የውስጥም የውጭም ታዛቢዎችን የሚያሳስት በመሆኑ ትኩረት የሚያሻው ጉዳይ ነው።
“የፀረ-ሽብር አዋጅ” የሚባለው ህገ-አልባነትን ህጋዊ ያደረገው ሰነድ የመንደር ካድሬዎች ሳይቀሩ አንድን ሰው በሽብርተኝነት “ጠርጥረው” ማሳሰርና ማስደብደብ አስችሏቸዋል። የአስተሳሰብ ድህነት ያጠቃቸው የህወሓት ካድሬዎች ብቻ ሳይሆኑ ኃላፊነት የጎደላቸው ፓሊሶችም የፀረ-ሽብር ህጉን ጉልበታቸውን ማሳያ እና ተፎካካሪዎቻቸውን ማጥቂያ አድርገውታል። በፀረ-ሽብር ህጉ ተከስሰው ወህኒ የወረዱ ዜጎችን ያጤነ ማንኛውም ሰው ኢትዮጵያ አገራችን በዚህ ህግ ሰበብ ምርጥ ዜጎቿን እያጣች እንደሆነ ይገነዘባል።
በሽብርተኝነት ለመጠርጠር የሚያበቁ ምክንያቶች እጅግ አሳዛኝ ናቸው። ለካድሬ ሰበካ እውነተኛነት ጥርጣሬውን የገለፀ አስተዋይ ሰው መሆን ብቻውን እንኳን በሽብርተነት ያስጠረጥራል። በዚህም ምክንያት ነው በእውቀትም በአስተሳሰብም የበሰሉ ዜጎቻን በአሸባሪነት የመፈረጅ እድላቸው ከፍተኛ የሆነው። የንቅናቄዓችን ዋና ፀሐፊ አቶ አንዳርጋቸው ጽጌን ጨምሮ በርካታ የሀገራችን ምርጥ ዜጎች የዚህ የተዛነፈ ትርጓሜ ሰለባ ሆነዋል። ተስፋ የሚጣልባቸው በርካታ ወጣቶች በዚህ ህገ-ወጥ ህግ እና የተሳሳተ ትርጓሜ ምክንያት የወጣትነት እድሜዓቸውን በእስር ቤት እንዲያሳፉ ተገደዋል። ከዚያ የበዙት ደግሞ በቃሉ ተሸማቀው፤ በሚያስከፍለው ዋጋ ተሸብረው ራሳቸውን እንዲደብቁ ተደርገዋል።
ለመሆኑ ኢትዮጵያ ያፈራቻቸው ምርጥ ዜጓቿ በአሸባሪነት ስም ወህኒ እየተወረወሩ ሲሰቃዩ ምላሻችን ምን ሊሆን ይገባል? እስከመቼ አስተዋይ፣ አርቆ አሳቢና አመዛዛኝ የሆኑ መሪዎቻችንን ለወያኔ ፋሽቶች እየገበርን እንኖራለን? ሀገራችን ይህን ኪሳራ የመሸከም አቅም አላት?
ግንቦት 7: የፍትህ፣ የነፃነትና የዲሞክራሲ ንቅናቄ ወያኔን ለማስወገድ የተሻለ ነው ብሎ ያመነበት የትግል ስልት – ሁለገብ የትግል ስልት ነው። በዚህ የትግል ስልት መሠረት ሕዝባዊ ተቃውሞ፣ ሕዝባዊ እምቢተኝነት እና ሕዝባዊ አመጽ ተደጋግፈውና ተናበው መሄድ አለባቸው ብሎ ያምናል። ስለሆነም እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ በአመቸውና በሚያምንበት መንገድ ለትግሉ አስተዋጽኦ የማበርከት እድል አለው።
በዚህም መሠረት ለሀገር፣ ለትውልድ ድህንነት ዋጋ ለመክፈል እና ለገዛ ራሳችን ህሊና ታማኝ ለመሆን በወያኔ “አሸባሪ” ለመባል መድፈር የትግላችን አንዱ አካል አድርገን መቁጠር ይኖርብናል። በወያኔ “አሸባሪ” መባል የሚያሸማቅቅ ሳይሆን የሚያኮራ፤ ለታላቅ ኃላፊነት እና ሕዝባዊ አደራ በእጩነት የሚያቀርብ መሆኑን በራሳችንም በማኅበረሰባችንም ውስጥ ማስረጽ ይኖርብናል። “አሸባሪ” የሚለው ቃል በወያኔ ተግባር መሠረት ሲተረጎም “ለሀገርና ለትውልድ ደህነት የሚጨነቅ ምርጥ ዜጋ“ ማለት እንደሆነ ማስተማር ይገባናል።
ወያኔ ወደ ሕዝብ የሚወረውረውን ጦር መልሰን ወደ ራሱ መወርወር ይኖርብናል። ወያኔ አሸባሪነት ዜጎችን ለማጥቂያ እያዋለው መሆኑ ተረድተን እኛ በዚህ ስያሜ መሸማቀቅ ሳይሆን፣ መኩራትና መልሰን ወያኔን ማሸማቀቅ ይኖርብናል። በውጭ አገራት እየተስፋፋ የመጣው የወያኔ ሹማምንትን የማሸማቀቅ ዘመቻ በኢትዮጵያ ውስጥም መጀመር ይኖርበታል።
ሕዝባዊ ተቃውሞ፣ ሕዝባዊ እምቢተኝነትና ሕዝባዊ አመጽ ሲቀናጁ ድላችንን ያፈጥናሉ። በወያኔ “አሸባሪ” መባል የመልካም ዜግነት ምስክርነት እንደሆነ በሙሉ ልባችን እንቀበል።
ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!