Monday, October 22, 2012

በረከት ስምዖን በኤርትራ ፓልቶክ ክፍል (ተስፋዬ ገብረአብ)

የኤርትራውያን የአረብኛ ፓልቶክ ክፍል በረከት ስምኦንን እንግዳ አድርጎ ጋብዞ ነበር። ጥያቄዎች ይቀርቡ የነበሩት በአረብኛ ቢሆንም፣ የትግርኛ ትርጉም ስለነበረው ሙሉውን ተከታትዬው ነበር። ውይይቱ ሲጨመቅ በሁለት መሰረታዊ ጥያቄዎች ዙሪያ ያተኮረ ነበር ማለት ይቻላል።

የመጀመሪያው፣ “የኢትዮ - ኤርትራ ድንበር ለምን አይካለልም? ችግራችሁ ምንድነው?” የሚል ነበር። በረከት የተለመደውን ምላሽ ሰጥቶአል።

“ርግጥ ነው ወደ ፍርድ ቤት እንሂድ ያልነው እኛ ነን። ፍርድ ቤትም ሄደን ተሸንፈናል። ምንም እንኳ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ ስህተት ነው ብለን ብናምንም፣ ውሳኔውን ከማክበር ውጭ አማራጭ የለንም። ችግሩ ያለው አፈፃፀሙ ላይ ነው። እንነጋገር ብለን ጠየቅን። የኤርትራ መንግስት ግን ፈቃደኛ ሳይሆን ቀረ። መነጋገር የሚያስፈልገን ጉዳዩ በቀጥታ ህዝብን የሚነካ በመሆኑ ነው። አንድን ቤት ለሁለት የሚከፍል ሁኔታ ጭምር አለ። ሌላው ጉዳይ ድንበሩን ማካለል ብቻ ሳይሆን፣ በሁለቱ አገራት መካከል ዘላቂ ሰላም የሚመጣበት ሁኔታ ላይ መነጋገር እንፈልጋለን። የንግድ ግንኙነት አለ። የህዝብ ግንኙነት ጉዳይም አለ። ህግደፍ ይህን ለመፍታት ፍላጎት የለውም። ከዚህ ባሻገር የኢትዮጵያ ያልሆነ መሬት ወደኛ እንዲመጣ ፍላጎት የለንም። ባድመ ላይም የተለየ ፍላጎት የለንም። የኛ ሆኖ ሳለ በህግ የተወሰነብንንም ቢሆን የመስጠት ችግር የለብንም። ጥያቄያችን ‘እንነጋገር’ የሚል ነው” ሲል መልስ ሰጥቶአል።

ሁለተኛው መሰረታዊ ጥያቄ፣

“እኛ ኤርትራውያን የታገልነው ለኤርትራ ነፃነት ነው። የሃይማኖት፣ የቋንቋ እና የብሄር ችግር የለብንም። የኢትዮጵያ ሁኔታ እና የኛ ተመሳሳይ አይደለም። ኢትዮጵያ ላይ የኦሮሞ እና የኦጋዴን ጥያቄዎች አሉባችሁ። ‘እስከመገንጠል’ የሚለው አንቀጽ ለናንተ ያስፈልግ እንደሁ አናውቅም። የኤርትራን አንድነት ችግር ላይ የሚከተውን የመገንጠል እና በብሄር የመደራጀት ነገር ወደኛም የምትገፉብን ለምንድነው? ኤርትራውያንን ለምን በጎሳ ለማደራጀት ትሞክራላችሁ? መገንጠልን እንደግፋለን ትላላችሁ። ኦጋዴኖች መገንጠልን ሲጠይቁ ግን አልፈቀዳችሁም። ለራሳችሁ ያላመናችሁበትን ወደ ኤርትራ ትገፉታላችሁ…”

የስምኦን ልጅ በረከት፣ ይህችን ጥያቄ ለመመለስ በጣም ብዙ ደከመ፣

“…የኤርትራ ህብረተሰብ ውስጥ ጥያቄው አለ” ሲል ጀመረ፣ “…እኛ ያመጣነው አይደለም። ተደራጅተው የመጡትን ግን እውቅና ሰጥተናል። በትግርኛ እና በትግረ፣ በአፋር እና በትግርኛ መካከል ቅራኔ አለ። የብሄር ጭቆና አለ። ይህ የማይካድ ነው። እርግጥ ነው፣ ትግሉ የተካሄደው ኤርትራ በሚለው ስሜት ነው። ኤርትራ ነፃነቷን ካገኘች በሁዋላ ግን ትግሉ ወደ ውስጥ ዞሮአል። ይህ የውስጥ ትግል ኤርትራን ይፈረካክሳታል ወይም ደግሞ አንድነታን ያረጋግጥላታል። ውስጣዊ ትግሉ ገና አልተፈታም። የኢትዮጵያን ሞዴል ውሰዱ አላልናችሁም። በቋንቋ እና በሃይማኖት ተበድለናል’ ብለው ወደኛ የሚመጡትን ግን እናግዛለን። የመገንጠልን መብት እንደግፋለን። እውነት ነው። እናበረታታለን ማለት ግን አይደለም። ኦጋዴን ላይ መገንጠልን የጠየቀው አንድ ፓርቲ ብቻ ነው። ህዝቡ እስካሁን የመገንጠል ዝንባሌ አላሳየም። ኤርትራ ተገንጥላለች። ልክ እንደ ኤርትራ አንድ ላይ መኖር ከማይቻልበት ደረጃ ላይ ከተደረሰ ሌሎችም ሊገነጠሉ ይችላሉ። ‘ኤርትራውያን አንድ ነን። ልዩነት የለንም፣ አንድ አገር - አንድ ልብ’ የሚለው ዘፈን ግን የሻእቢያ መንገድ ነው።”

በዚህ የበረከት ንግግር ኤርትራውያን መቆጣታቸውን ተከታትዬአለሁ።

በመጨረሻ፣ “በረከት ስምኦን አንተ ትውልድህ ከኤርትራ ነው። ለመሆኑ በኢትዮጵያ የመንግስት ከፍተኛ ስልጣን ላይ በመቀመጥህ የደረሰብህን ችግር ልትነግረን ትችላለህ?” የሚል ጥያቄ ለበረከት ቀርቦለት ነበር። ለመመለስ ፈቃደኛ ሳይሆን ቀረ። የታዳሚዎችን የቁጣ ስሜት የተገነዘበው በረከት፣ ውይይቱን ለማቋረጥ ተገደደ። በርካታ ጋዜጠኞች ጥያቄ ለመጠየቅ እጅ አውጥተው የነበረ ቢሆንም በረከት አስቸኳይ ስራ እንዳለው ገልፆ መካከሉ ላይ ተሰናብቶአል።
ተስፋዬ ገ/አብ

No comments:

Post a Comment