Friday, October 26, 2012

የአገር አቀፉ የኢደል አድሐ ቢጫ ተቃውሞ ሙሉ ዘገባ

ህዝበ ሙስሊሙ ዛሬም በከባድ ቁጣ ታጅቦ በመላው ሃገሪቱ በዒድ አደባባዮች ተቃውሞውን ሲያሰማ ዋለ፡፡ ይህ በሃገራችን በአይነቱ የመጀመሪያ የሆነው ህዝባዊ ተቃውሞ አካል የሆነው የኢዱል አድሃ የቢጫ ማእበል ‹‹ሁሉም የሚመለከታቸው አካላት ቆም ብለው እንዲያስቡ›› በሚል የቢጫ ተቃውሟችንን ደጋግመን እንደምናሰማ በተገለፀው መሰረት በመላ ሃገሪቱ በሚሊዮኖች ከጫፍ እስከ ጫፍ ተካሂዷል፡፡ (የቢጫው ተቃውሞን ትርጉምና ዓላማ ለመረዳት በድምጻችን ይሰማ ላይ የተስተናገደውን ‹‹የቢጫው ተቃውሞና አገራዊ መልእክቱ›› የሚለውን ጽሑፍ ይመልከቱ) ሚሊዮኖች በተሳተፉበት በዛሬው ቢጫ ተቃውሞ ከዚህ

በፊት በሰፊው ይባሉ ከነበሩት ‹‹ድምፃችን ይሰማ! ኮሚቴው ይፈታ! የታሰሩት ይፈቱ! እና ምርጫችን በመስጂዳችን!›› ከሚሉ የድምፅ መፈክሮች በተጨማሪ በርካታ አዳዲስ መፈክሮችን ህዝቡ አሰምቷል፡፡ ‹‹የህገ መንግስቱ አንቀፅ 27 ይተግበር! መብታችን ይከበር! ጭቆናው በቃን! ማስገደድ በቃን!›› እና ሌሎችም በእለቱ ከተስተጋቡ መፈክሮች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ የመብት ጥያቄያችንን አስመልክተው የሚነዙ ፕሮፖጋንዳዎች ከመንግስት ሚዲያና የመሰብሰቢያ አዳራሽ ፍጆታነት ውጭ ከንቱ መሆናቸውን ዳግም በገሃድ ያሳየም ነበር፡፡በአዲስ አበባ በመቶ ሺዎች የደመቀው የተቃውሞ ትእይንት በከተማው በሁሉም አቅጣጫዎች በቢጫ ማእበል የተዋጠ ነበር፡፡ በስታዲየም ውስጥ፣ በአብዮት አደባባይ፣ በኢቲቪ ህንፃ፣ በፌደራል ፖሊስ ዋና መስሪያ ቤት ፊት ለፊት የተለየ ቁጣ አዘል ተቃውሞ ተስተጋብቷል፡፡ እስከአሁን ባሰባሰብነው መረጃ ከምስራቁ የሃገራችን ክፍል በሃረር ኢማም አህመድ ስታዲየም፣ ከዛም አልፎ እስከ ጀጎል የሞላው ህዝብ ደማቅ ተቃውሞ ያሰማ ሲሆን ‹‹ክርስቲያኖች ወንድሞቻቸን ናቸው›› ሲሉም ሃገራዊ ፍቅራቸውን ገልፀዋል፡፡

በአዳማ የመብት ጥሰቱ ድንበር ማለፉን በከባድ ተቃውሞ የገለፁ ሲሆን ከጅምሩ እስከ ማብቂያው ሙሉ ከተማው በቢጫ የደመቀ ህገወጥ ምርጫንና የመሪዎቻችንን መታሰር ያወገዘ የድምፃችን ይሰማ ተቃውሞ ተካሂዷል፡፡ በድሬዳዋ እና በአፋር ሚሌም የታሰሩትን አላህ እንዲያስፈታቸው በኢድ አደባባይ ዱዓ ተደርጓል፡፡ በሰሜኑ የሃገራችን ክፍል በደሴ ‹‹በአህባሽ ኢማም አንሰግድም›› በሚል ህዝቡ በራሱ ኢማም በመስገድ ታሪካዊውን ቢጫ ተቃውሞ በተለመደው ጀግንነቱ አስተጋብቷል፡፡ በከሚሴም ከእስከዛሬዉ ለየት ባለ ሁኔታ ወደ 80 ሺ የሚጠጋ ህዝብ በአአካባቢው ከሚገኙ 7 ቀበሌዎች እና ከከሚሴ ከተማም ጭምር በመውጣት ትላልቅ ባነሮችና መፈክሮች በመያዝ በቢጫ የታጀበ ከፍተኛ የተቃዉሞ ድምፅ አሰምተዋል፡፡ በባቲ፣ በመርሳ፣ በወልዲያ እና ሌሎች ከተሞችም ሃገራዊ ተቃውሞው የሁሉም መሆኑን በድምቀት አውጀዋል፡፡ በሰንበቴም ከ5 ሺህ በላይ ህዝብ በኢድ ሰላት ላይ ደመቀ ተቃውሞ አሰምቷል፡፡ በሌላ በኩል በትግራይ አንዳንድ ከተሞች ህዝበ ሙስሊሙ እቤት በመቅረት መቃወሙን ምንጮቻችን ዘግበዋል፡፡ በምእራቡ የሃገራችን ክፍልም በጅማ ከሰላት በፊት የተጀመረው ከባድ ቁጣና ተቃውሞ ህዝቡ በሚሰማቸው ዳዒዎች መስመር እንዲይዝ የተደረገ ሲሆን ህዝቡም ለሚያምነው የተገራ፣ በመብቱም የማይደራደር መሆኑን አሳይቷል፡፡ በበደሌም ከፍተኛ ተቃውሞ ተካሂዷል፡፡ በኢሊባቡር ከመቱ 42 ኪ.ሜ ርቃ በምትገኘው አልጌሳቻ ወረዳ ሙሉ የከተማውና የገጠሩ ማህበረሰብ እጅ ለእጅ በመያያዝ ምርጫው እንደማይወክላቸው በመግለፅ ‹‹ድምፃችን ይሰማ!›› በሚል ተቃውመዋል፡፡ በደቡብ የሃገራችን ክፍል ከዚህ በፊት በጉራጌና ስልጤ ዞኖች፣ እንዲሁም በዲላ የተካሄዱት አይነት መሰል ተቃውሞ እንደሚካሄድ የሚጠበቅ ሲሆን ምንጮቻችን እንዳደረሱን እንዘግባለን፡፡ ወራቤ ላይ የመንግስት ተወካዮች ንግግር ለማድረግ በሞከሩበት ሰአት በተቃውሞ ሲያስቆሙት በወሊሶ እቤት በመቅረት ተቃውሞአቸውን ገልፀዋል፡፡ ከጁምኣ ሰላት በኋላ ግን በመስጊዶቻቸው እጅግ በርካታ ህዝብ በተገኘበት ተደርጓል፡፡ በሻሸመኔም ህዝቡ ከፍተኛ የሆነ ተቃውሞ አሰምቷል፡፡ እስከአሁን ባለው መረጃ ብቻ በመላ ሃገሪቱ በአራቱም አቅጣጫዎች ህዝብ ‹‹መብቴ ይከበርልኝ! ወኪሎቼ ይፈቱ!›› በማለት የአላማ ፅናቱን ያሳየ ሲሆን ለህገወጥ ምርጫና ለህገወጥ ተመራጭ ምንም እውቅና እንደማይሰጥ በማያዳግም ሁኔታ አቋሙን ገልጧል፡፡

በአጠቃላይ የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በፓርላማ ለመላው ሙስሊሞች ‹‹ምርጫውን በፈለጋችሁት መሰረት በሰላም በማከናወናችሁ እንኳን ደስ አላችሁ!›› ሲሉ ከጥቂቶች በስተቀር ብዙሃኑ መደሰቱን በገለጹበት ማግስት መላው የሃገራችን ሙስሊም ‹‹ምርጫው አይወክለኝም!›› በሚል መቃወሙ መንግስት እየተከተለው ያለው አካሄድ ከህዝብ ልቦና የሚያርቀው መሆኑን አመላካች ነው፡፡ ‹‹ኮሚቴዎቻችን ይፈቱ!›› ሲል በፊርማው የወከላቸው መሪዎቹ ለእስር ተዳርገው የሚያስቆም ህሊና እንደሌለው መላው ሙሰሊም ህዝብ ተአምር በሚያስብል ፅናት እየገለጸ መሪዎቻችንን ከህዝቡ በመነጠል የተለየ አጀንዳ ያነገቡ ለማስመሰል የሚደረገው ሩጫ ውሃ የማይቋጥርና የማይሳካ መሆኑን መስማት ለሚችል ሁሉ አስተጋብቷል፡፡ ህዝብ መብቱን ለማስከበር ሊከተል የሚገባውን ትልቁን ሰላማዊ አካሄድ እያደረገ ባለበት ሁኔታ መንግስት ሊወጣ የሚገባውን ሃላፊነት መዘንጋት እንደሃገር የመልካም ነገር መገለጫ አይደለም፡፡

በመጨረሻም የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቪዥን ድርጅት ወትሮ የሚያቀርበውን የቀጥታ ስርጭት ማቅረብ ባይሳካለት አንኳ እስከ 8 ሰአት ድረስ ዜና መዘገብ አለመቻሉ የመንግስትን የአፈና አካሄድ ህዝባዊ ድጋፍ እንዳለው አድርጎ የማቅረቢያ ጠባብ አማራጭ እንኳን ማጣቱን ያመላክታል፡፡ በዚህም ህዝባዊ ተቃውሞው የመላው ሙስሊም ኢትዮጵያዊ መሆኑን መንግስትም ሆነ ኢቲቪ በተዘዋዋሪ መንገድ ምስክርነታቸውን ሰጥተዋል፡፡ ቅጥፈት የማይሰለቸው ኢቲቪ ግን በ 8 ሰአት የዜና እወጃው ይህን በሚሊዮኖች የሚቆጠር መብት ጠያቂና ሌሎች ሚሊዮኖች ታዛቢዎችን ‹‹አይናችሁ በትክክል አላየም›› ለማለት በሚመስል ሁኔታ ‹‹አንዳንድ ግለሰቦች በሽብር ወንጀል ተጠርጥረው ጉዳያቸው በፍርድ ቤት እየታየ የሚገኙ ግለሰቦች ይለቀቁ ሲሉ ጠይቀዋል›› ሲል ውሸት እንዲሰለቸን ባደረገው መስኮቱ ብቅ ብሎ የተለመደ ተግባሩን ፈፅሟል፡፡
ምንም አንኳን ህዝበ ሙስሊሙ የመበት ትግሉ እልህ አስጨራሽ ሊሆን እንደሚችል በማመን በሰላማዊነቱ መፅናትን ቢመርጥም ዛሬም የተለያዩ ትንኮሳዎች ሊፈፅሙበት ተሞክረዋል፡፡ በተለይ በአዳማ መደበኛው የዒድ ተቃውሞ ከተጠናቀቀ በኋላ ሆን ተብሎ በተፈጠረ ትንኮሳ ግርግር በመከሰቱ በርካታ ሰዎች መታሰራቸውና መደብደባቸውን ለማወቅ ችለናል፡፡ በተለይም የፌዴራል ፖሊስ በአዳማ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ላይ ከፍተኛ ድብደባና እስር ያካሄዱ ሲሆን ህዝቡ ግን መሰል ስቃይ ከመብት ትግል ሂደቱ እንደማይገታው በተግባር አሳይቷል፡፡ በአዲስ አበባ ሰላትን አስቀድሞ በመስገድ፣ የድምፅ ማጉያውን በስታዲየም ውስጥና በተወሰነ መልኩ በሴቶች አካባቢ እንዲሰማ ብቻ በማድረግ፣ ፖሊሶች በመገናኛ ሬዲዮ ‹‹ሃይል ይጨመርልን›› በሚል ህዝብ ውስጥ ፍርሃትን ለመልቀቅ በመሞከር የህዝቡን የጋራ ተቃውሞ አንድነትና ውበት ለማሳጣት ቢሞክሩም ደማቁን ተቃውሞ ግን ለደማቅ ታሪክነት ከመብቃት አላገዱትም፡፡

በመጨረሻም ለዲን ባለው ንፁህ ተቆርቋሪነትና ለወከላቸው ንፁህ መሪዎቹ ያለውን አጋርነት ለህይወቱ እንኳን ሳይሳሳ በፅናት እየገለፀ ያለው መላው ህዝባችን ዛሬም ሆነ መቼ ወደር ለማይገኝለት ድንቅ ታሪኩ አላህ ምንዳውን እንዲከፍለው እንለምናለን፡፡ በሰላማዊ ትግል መንገድ ላይ አቀበት መብዛቱን ተረድቶ እየተበደለም በሰላም በመፅናት በተለይም በዛሬው ውሎ በወጣው መርሃግብር ተቃውሞውን በማሰማትና ከፀጥታ ሃይሎች ጋርም ለሰላም በመተባበር ላሳየው አገራዊ ሃላፊነት ምስጋና ሊቸረው ይገባል፡፡ የመንግስት አካላትም መብትን መጠየቅ የዴሞክራሲ አንዱ መገለጫ ነውና በዛሬ ውሎ ያሳያችሁን አንፃራዊ በጎ የሃላፊነት ስሜት እሰየው የሚያስብል ሲሆን የተጠየቀን ጥያቄ መመለስም ሃላፊነታችሁ መሆኑን ልናስታውስ እንወዳለን፡፡ ድምፃችን ይሰማ ገጽ የዒዱን ተቃውሞ የቀጥታ ዘገባ (Live blog) መስራቷ ለህዝበ ሙስሊሙ ትክክለኛውን መረጃና ከአሚሮቻችን የሚሰጥን አቅጣጫ ለማስተላለፍ ያላትን ቃል ዳግም ያረጋገጠችበት ሆኖም ቀኑ አልፏል፡፡ ዛሬም በህዝቡ መሰል ቁርጠኝነት እና ፅኑ አቋም የትግል ጉዟችንን ዳር እናደርሳለን፡፡

ድል ለኢትዮጵያ ሙስሊም!
አላሁ አክበር!

No comments:

Post a Comment